Thursday, July 3, 2014

(ሰበር ዜና) የየመን መንግስት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን አሳልፎ ሰጠ

andargachew( የደረሰን ዜና እንደሚያመለክተው፣ የግንቦት ሰባቱ ዋና ጸሃፊና የድርጅቱ ሞተር የሚባሉት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ  ለኢትዮጵያ መንግስት አሳልፈው ተሰጥተዋል። አቶ አንዳርጋቸው ለትራንዚት ሰንዓ የመን በቆዩበት ጊዜ በየመን ደህንነት ሃላፊዎች  ከአሥር ቀናት በፊት የታገቱ ሲሆን፣ ድርጅታቸው ግንቦት ሰባት እርሳቸዉን ለማስፈታት ዉስጥ ዉስጡን በርካታ ጥረቶች ሲያደርግ እንደቆየም ከድርጅቱ የወጣዉ መግለጫ ይጠቁማል።
አቶ አንዳርጋቸውን ለመጎብኘት ጥረት ያደረገው የእንግሊዝ ኤምባሲ፣ በየመን አቶ አንዳርጋቸውን ለማግኘት እንዳልቻለ የገለጸዉ የደረሰን ዘገባ፣ አቶ አንዳርጋቸው ለኢትዮጵያ መንግስት አሳልፈው የተሰጡት፣ በየመን መንግስት መያዛቸው በድርጅታቸው ለሕዝብ ይፋ ከመሆኑ በፊት እንደሆነም ለማረጋገጥ ችለናል።
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ከግንቦት ሰባት አባላት ዉጭ በበርካታ ኢትዮጵያዉያን ዘንድ በቆራጥነታቸውና ሐሳብ አመንጪነታቸው የሚታወቁ ናቸው። በምርጫ ዘጠና ሰባት ወቅት ፣ በቅንጅት ዉስጥ ትልቅ ተሳትፎ ያደርጉ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው፣ ለሰላማዊ ትግሉም መጽሃፍ ጽፈው ያበረከቱ አገር ወዳድ ሰው ናቸው። በወቅቱ የኢሕአዴግ መንግስት አቶ አንዳርጋቸውን በዝዋይ አስሮ የነበረ ሲሆን፣ በዚያም በደረስባቸው ድብደባ አይናቸው ላይ ጉዳት እንደደረሰም በወቅቱ መዘገቡ ይታወሳል። አቶ አንዳርጋቸው አገዛዙ በሰላም አይወርድም በሚል ሁለገብ ትግል አደርጋለውሁ የሚለው የግንቦት ሰባት ከፍተኛ አመራር አባል ሆነው ሲሰሩ የነበሩ ታጋይ ናቸው።

No comments:

Post a Comment