Wednesday, December 16, 2015

የመጨረሻው ድል የፍትህ: የሰላም፡የፍቅር ነው። በዘር በክልል መከፋፈል ከመለስ ጋር ሞቷል



ቢላል አበጋዝ
ዋሽግተን ዲ ሲ
ረቡዕ ፣ ዲሴምበር 16 ቀን 2015
እንደዛሬው ወያኔ ኢህአዴግ ከመቸውም ጊዜ በበለጠ ግልጽ በሆነ መንገድ ፍላጎቱን በትክክል፤ የሚሄድበትን መንገድ ወለል አርጎ ያሳየበት ጊዜ የለም።ፍላጎቱ ስልጣን፤ዘዴው በጭካኔ መርገጥ፤ ይህ ካልሰራ አገር መበተን ነው።ይህን ማንም አሽቃባጩ ማንም ይቅርታ ጠያቂው ሊከላከልበት የሚችለው አይደለም።ከዚህ ወዲያ በጭካኔ የመርገጥ ተግባሩን ይበረታበታል እንጂ የሚቀንስው አይደለም።የህዝቡን እምቢተኝነት “የሽብርተኛ” ማለቱ የምዕራቡን ዓለም እገዛ ለማግኘት፤ከተጠያቂነትም የሚድን መስሎት ነው።

abebe Gelaw

የህወሃት ማከላዊ ኮሚቴ በሁለት ተከፍሎ ይህም ማለት ለህዝቡ እምቢተኝነት ፖለቲካዊ መፍትሄ መስጠትና እንደወትሮው በጭካኔ መርገጥ ላይ ቢዶልት፤ጨፍጭፍ፤ እርገጥ የሚለው ክፍል ያቸነፈ መሆኑ በኦሮሚያ ወታደራዊ አዋጅ መታወጁ አመላካች ነው።የሚሄድበትን መንገድ ወለል አርጎ ያሳየበትም ይኸው ነው።
ህዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሀይሎች ዛሬ የሚሰሩት ስተት ቢኖር በኦሮሞ ኢትዮጵያ የተነሳውን አመጽ አንዱ ክፍል የተወሰነ፤የኦሮሞ ብቻ አድርጎ ማሰብ፤ኦሮሞች የሆኑ ደግሞ የብቻ ትግላቸው አድርገው ካዩት ነው።እኒህ ዳር ና ዳር ያሉ የጽንፈኝነት ሰለባ አመለካከቶች ለወያኔ የሚመቹ የኢትዮጵያን ህዝብ ለቀጣይ ባርነት ይሚዳርጉ ናቸው።የወያኔ ኢህአዴግ ፍላጎቶችች ጋር የሚናበቡ ጽንፎች ናቸውና።
የህዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ትግል መራመድ እነዚህን ከላይ ያነሳኋቸውን ጽንፈኝነቶች እያከሸፈ ወያኔ ጋር መጋፈጥ ይኖርበታል። ደስ የሚያሰኘው ወጣቱ እኒህን ጽንፎች እያከሸፈ መሆኑ ነው። እኒህ ጽንፎች በኦሮሞው በኩል የዛሬው ጉዳት፤ሞትና ስቃዩ ላይ ትኩረት ከማድረግ ይልቅ ያለፈ ታሪክን ይዘው ለጥርጣሬ በር ይከፍታሉ።በአማራው በኩል ያሉት ጽንፈኞች ደግሞ አማራው ሲበደል ኦሮሞው መቸ አገዘ ይላሉ።በዚህ ክርክር የጋምቤላው የአፋሩ የሶማሉ የደቡቡ በደል መነሳቱ ይቀራል።በዚህ መሃል ወያኔ ኢህአዴግ ፋታ ያገኛል ማለት ነው።ወያኔ ኢህአዴግን የሚጥለው አገር አቀፍ ህዝባዊ አመጽ ነው።አንድ ባንድ ተራ በተራ ለገጠሙት ብርታት የለውም ማለት ወያኔ ላይ የዋህ ግምት ማድረግ ነው።
ወያኔ ኢህአዴግ በህዝቦች መካከል ክፉ ልዩነቶችን ቢያጣ እራሱ በጥረቱ ያሰናዳቸዋል።ይቀምማቸዋል።በጎንደር እያደረገ ያለውን በክልል ውስጥ ክልል መፍጠርን፤የቅማንት ህዝብን ጥያቄ ማራገብን ማመልከት ብቻ ይበቃል።እንዲህ ያሉትን ዘዴዎች ትቶ ለምን ከነጭርሱ ኤርትራ ወረረችኝ አይልም ?ይህንም ይላል።ግን ትልቅ ካርዱ ሰለሆነ ያቆየዋል። ኤርትራን ይተነኩስ እንደሆን እንጂ ኤርትራ ኢትዮጵያን የምትወርበት ምክንያት ዛሬ የለም።ኤርትራ የኢኮኖሚ ችግርዋን መልክ ማስያዝ ላይ እንዳለች እየተነገረ ከሆነ ቆይቷል።
አፍጥጠው ያሉት የቀይ ባህር ባሻገር ሀብታም አረብ አገሮች ዛሬ ወያኔን በገለልተኝነት አቌም ያዩታል እንጂ ለወያኔ ኢህአዴግ መሰናበት አይጨነቁም።እንዲያውም በኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ አገር ወዳድ መንግስት ሳይቆም የኔ የሚሉት ሀይል ከዚህ ወያኔ ሊያራግበው ከሚመኘው እሳት መሃል እንዲወጣላቸው የኢትዮጵያን ጉዳይ መያዣ እዲኖራቸው ይፈልጋሉ።ይህን ደግሞ የሚገልጸው ከየመን በኋላ ሀብታም አረብ አገሮች ፈርተዋል።ሰግተዋል።ምንም ከማድረግ አይመለሱም።ኢትዮጵያ የወትሮ ምኞታቸው፤የወትሮም ስጋታቸው ናትና። የህዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ትግሉን የሚያዛንፉ ሌላ ሀይሎች እነሱ ናቸው እላለሁ።ጠላት ወያኔ ኢሃዴግ ብቻ አይደለም።
ዛሬ በኢትዮጵያ ወያኔ ህወሃት በግድያ፤ በድብደባ ሊገታው የማይችለው አመጽ ተነስቷል።ከኢትዮጵያ ውስጥም ይሁን ከውጭ ዜጎች ስጋት ባለበት መንፈስ ሁኔታውን እየተከታተሉ ነው። የወያኔ የፖሊስና ወታደራዊ ሀይል በትንሹ እንኳን ቢነቃነቅ የወያኔ ህልውና የመጨረሻዎቹ ሰዓቶች መድረሳቸው አመላካች ነው።ወያኔ ይህን ያህል በቋፍ ነው። ያውቀዋል።ጥያቄው የአሁኑ የየካቲት 1966 ዓም ድጋሚ ይሆን ? ነው።
ወያኔ መግደል ይችላል።የኢትዮጵያ ህዝብ የነጻነት የዴሞክራሲ ትግል ሊገታ ግን አይችልም።የፋሺስት ኢጣሊያ ጭፍጨፋን ታዝቦ ለታሪክ ያቆየው አንድ የሁንጋሪያ ሰው የፋሺስ ኢጣልያ የአረመኔ ድርጊት ኢትዮጵያ በሚለው መጽሀፉ መጨረሻ እንዲህ ብሏል “በደምና በስቃይ ላይ የተገነባ፤በደምና በገጠጠ ውሸት ላይ የተመረኮዘ ይወድቃል።ከመቸውም ጊዜ በበለጠ የመጨረሻው ድል የፍትህ: የሰላም፡የፍቅር ነው።”
ድል ለዲሞክራሲያዊ ሀይሎች ሁሉ!
ኢትዮጵያ በአንድነትዋ በነጻነት ለዘለዓለም ትኑር

No comments:

Post a Comment