Tuesday, October 21, 2014

የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ችሎት ትናንት እና ዛሬ ቀጥሎ ዋለ

የመከላከያ ምስክሮች በዋና ዋና ጭብጦች ላይ የኮሚቴዎቹን ንጹህነት እየመሰከሩ ነው!
ድምፃችን ይሰማ እንደዘገበው:-
የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ችሎት ትናንት እና ዛሬ ቀጥሎ ውሏል፡፡ ችሎቱ ባለፈው ዓመት ጀምሮት የነበረውን የመከላከያ ምስክሮች ሂደት አቋርጦ በዚህ አመት ዳግም ቢጀምርም ከጥቅምት 3/2007 ጀምሮ ‹‹ኤሌክትሪክ ሄዷል፣ ኤሌክትሪክ ተቆረጠ››፣ እንዲሁም ‹‹ካርድ አልተሞላም›› በሚሉ ምክንያቶች ችሎቱ ከሳምንት በላይ ለሆነ ጊዜ ድጋሚ እንዲቋረጥ ሆኖ ነበር፡፡ ዛሬ ችሎቱ ዳግም ሲጀመር ባለፈው የመከላከያ ምስክርነታቸውን ጀምረው መስቀለኛ ጥያቄ ሳይቀርብላቸው በቀሩት አቶ አህመድ ኡመር ሲጀምር ምስክነርት በሰጡበት በጭብጥ 10 ላይ አቃቤ ህግ ለመከላከያ ምስክሩ አቅርቦ ያልጨረሳቸውን መስቀለኛ ጥያቄዎች አቅርቦ አቶ አህመድ ኡመር በቂ ምላሽ ሰጥተዋል።
muslim dim
አቶ አህመድ ኡመር 53ኛ ምስክር በመሆን በጭብጥ 11 ላይ ትናንት ምስክርነት ሲሰጡ በሐምሌ 2004 የመንግስት ታጣቂ ኃይሎች በህዝበ ሙስሊሙ ላይ የፈፀሙትን ጭፍጨፋ የገለጹ ሲሆን በታላቁ አንዋር መስጂድ በተደረገው የአንድነትና የሰደቃ ፕሮግራም ላይ ንግግር ያደጉት የህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ሕገ ወጥና ኹከት ቀስቃሽ፣ እንዲሁም ጸረ ሰላም ንግግር ሳይሆን ሰላማዊና ለህዝቦች የጋራ መኗኗር ጠቃሚ ሐሳብ ለህዝቡ ማስተላለፋቸውን ለችሎቱ አስረደትዋል፡፡ 54ኛ የመከላከያ ምስክር ሆነው የቀረቡት አቶ ጀማል ሽኩር ደግሞ በጭብጥ 7 ላይ ሰፊ ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡ በእማኝታቸው እሳቸው በሚኖሩበት ጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 የመጅሊስን ምርጫ አጠቃላይ ሂደት ሲመሩትና ሲያቀናብሩት የነበሩት የአካባቢው የወረዳ ሀላፊዎችና የፖለቲካ ሹመኞች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የቤት ለቤት ቅስቀሳውን ጨምሮም ሂደቱ በሙሉ በመንግስት አስፈጻሚዎች ይዘወር እንደነበርም ገልጠዋል፡፡
ዛሬ በቀጠለው ችሎትም የ3 መከላከያ ምስክሮች መከላከያ ምስክርነቶች የተደመጡ ሲሆን በ2004 ከተሰጡት የአዲስ አበባ ከተማ አህባሽ ስልጠናዎች ትልቁ በነበረውና በኢትዮ-ቻይና የሙያ ኮሌጅ በተካሄደው የጠመቃ ስልጠና ከሰልጣኞቹ አንዱ የነበሩት አቶ ሰኢድ ኢብራሂም በስልጠናው ሂደት ላይ የነበሩትን የመንግስት እጆችና ሕገ ወጥ አካሄዶች ሲያስረዱ ቀጣዩ ምስክር አቶ ሙሐመድ በሐምሌ 2004 የመንግስት ታጣቂዎች አንዋር መስጂድ ውስጥ ይገኙ በነበሩ ምእመናን ላይ የፈጸሙትን ጭፍጨፋ በጭብጥ 11 ማእቀፍ መሰረት ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡
ጋዜጠኛ አቡበከር አለሙ በተከሰሰበትና በፒያሳው ኑር መስጂድ ሰላማዊ ውይይት እንዳይካሄድ በማድረግና በማደናቀፍ ለተመሰረተበት ክስ አቶ አብዱልሃኪም አስፋው የመከላከያ ምስክርነት ሰጥዋል፡፡ በምስክርነታቸውም በወቅቱ አቡበከር ኹከት ፈጣሪ ንግግር እንዳልተናገረና የመንግስት ክስ ከሚለው በተቃራኒ በወቅቱ ሌሎች ሰዎች የተሰጣቸውን ጥያቄ የመጠየቅ መብት ሁሉ ተነፍጎ መድኩን ጥሎ ለመውጣት መገደዱን አስታውሰዋል፡፡ የዛሬዎቹ ምስክሮች በሰጡት ምሰክርነት ላይ ችሎቱ መስቀለኛ ጥያቄ አቅርቦላቸው በተገቢው መልኩ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ችሎቱ በነገው እለትም ሂደቱን ይቀጥላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በሌላ በኩል በአቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ ተከሰው በነጻ የተለቀቁት ሸኽ አብዱህራማን ኡስማን ከሊል እና አሊ መኪ በድሩ ዳግም ወደ ወህኒ እንዲገቡ በፌደራሉ ይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት እንደተወሰነባቸው ታውቋል፡፡ የፌደራሉ ከፍተኛው ፍ/ቤት 4ኛው ወንጀል ችሎት በታህሳስ 3/2006 በሰጠው ብይን ሁለቱን ተከሳሾች ጨምሮ 8 ሙስሊሞች አቃቤ ህጉ ካቀረበባቸው ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ውሳኔ ካስተላለፈ በኋላ አቃቤ ህጉ ባቀረበው ይግባኝ መሰረት ጉዳያቸው ሲታይ የቆዩት ሸኽ አብዱራህማን እና አሊ መኪ ድጋሚ እንዲታሰሩ ወሳኔ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ከህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ጋር ተከሰው ፍርዳቸውን ሲከታተሉ ቆይተው በነጻ የተሰናበቱት ሸኽ አብዱረህማን ኡስማን ከሊል እና አሊ መኪ በድሩ በፍርድ ቤት ድጋሚ እንዲታሰሩ በመወሰኑ ሸኽ አብዱረህማን አሁን በቂሊንጦ ወህኒ ቤት የሚገኙ ሲሆን ሌላው ወንድም አሊ መኪም በተገኘበት እንዲያዝ መባሉ ታውቋል፡፡ በዚህም መሰረት የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሰጠባቸውና በችሎቱ ተገኝተው የነበሩት ሸኽ አብዱረህማን ኡስማንም ችሎቱ እንደተጠናቀቀ በፖሊስ ተይዘው መታሰራቸውና አሁን በቂሊንጦ ዞን 3 እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምፃችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

No comments:

Post a Comment