Tuesday, November 11, 2014

“የምጣዱ እያለ የእንቅቡ ተንጣጣ”

አገሬ (ከስዊድን)፣ 2014-11-05
ይህን ፅሁፍ ለመፃፍ ያነሳሳኝ ዋናው ምክንያት በድረ-ገጽ ላይ ”ፕሮፌሰር መስፍንን ለቀቅ” በሚል ርዕስ በአቶ አንተነህ መርዕድ የተፃፈው ”አገም ጠቀም” የሆነና ሚዛናዊነት የጎደለው መጣጥፍ ከመቸውም በበለጠ ስለከነከነኝ ነው።
Pro Mesfin
አቶ አንተነህ እንዳሉት አንደኛ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም አይደለም ለራሳቸው፣ ለሌላም የሚተርፍ አንደበት አላቸውና ራሳቸው መልስ ይስጡ በማለ፤ ሁለተኛ ትልልቅ አገራዊ ጉዳይ እያለ በዚህ ጠባብ ነገር መጠመድ ለማን ይበጃል በሚል ቢተውት የተመረጠ ነበር። ነገር ግን ያን በማለታቸው ልክ አለመሆናቸውን አምነውበት ለንባብ ያበቁት መጣጥፍ ለፕሮፌሰር መስፍን ለመወገን ሲሉ ብቻ የአማራውን ነገድ «አለ ወይስ የለም?» ማለት እንደማይረባ ጉዳይ ቆጥረውታል። ነገር ግን በተለይ በአሁኑ ሰዓት አማራ እንደሰባዊ ፍጡር ሳይቆጠር ደመከልብ ሆኖ አጥንቱን ከስክሶ ደሙን አፍስሶ ባቆማት አገር እንዳይኖር በሚደረግበት ወቅት ”እንቶ ፈንቶ” ሲሉ ማጣጣል ትልቅ ስህተት ይመስለኛል።
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ባቋቋሙት «የኢትዮጵያ ሰብዐዊ መብት ጉባኤ (ኢሰመጉ)»፣ እርሰዎ እንደሚሉትና የኢትዮጵያም ህዝብ ተረድቶት እንደነበረው በወያኔ አገዛዝ ለሚደርሰው ገፍና በደል አለኝታ ለመሆን አልነበረም። ይልቁንም ከፕሮፌሰር መስፍን ከአንደበታቸው እንደሰማነው ከሆነ ኢሰመጉን ያቋቋሙት ወያኔን ለመርዳት መሆኑን ሰለሰማን የርስዎ የመከራከሪያ ነጥብ ”ከባለቤት ያወቀ ቡዳ ነው” የሚሉት አይነት ይሆንብዎታል። አቶ አንተነህ በውነቱ እርሰዎን ቅር ማሰኘትም ሆነ ፕሮፌሰር መስፍንን የመዝለፍ ሀሰብ በ አይምሮየ የለም ግን ፕሮፌሰር መስፍን የሚነግሩንና የሚሰሩት ነገር ካልተጣጣመ ቃልን ከተግባር በማጣጣም የምናስታርቀው ምን ብንል ነው፧ ፍርዱን ለርስዎ እተዋለሁ።
የአማራን ጉዳይ በተመለከተ አቶ አንተነህ እንደተረዱት ፕሮፌሰር መስፍን የወያኔውን መሪ መለስ ዜናዊን «አማራ የለም» ብለው «ዘረኝነት እንዳይስፋፋ አደረጉ» የሚል አስተያየትዎ እደተጠበቀ ሆኖ፣ እኔ ደግሞ ከአንድ ታዋቂ ግለሰብ መወቀስ ይበልጥ የኢትዮጵያ አገራችንና በህዝቧ ላይ የወደቀው የመከራ ቀንበር እጅጉን ያመኛል። ከወያኔ ወደ ስልጣን መምጣት ትንሽ ቀደም ብሎ ጀምሮ ያደረጓቸውን ድርጊቶች ላስታውስዎ፦
ፕሮፌሰር መስፍን እኤአ 1991ዓ.ም ለንደን ላይ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን በራሳቸው ፈቃድ ወክለው ከነወያኔና ከነኦነግ ጋር ተደራድረው ድጋፍ በመሆን አስገቡዋቸው።
የኢትዮጵያ ህዝብ «መጣብን» ብሎ የፈራውን የዘረኝነት አገዛዝ የተከበሩ ፕሮፌሰር መስፍን በግልፅ በአደባባይ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በተለይም አማራን እንደህዝብ ከሚጠላው የወያኔ መሪ ጋር በማነጋገራቸው ወያኔን እውቅና እንዲያገኝ አደረጉ።
ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ፣ የዘረኝነት አባዜ ይዟቸው ሳይሆን ተገደው፣ ለአማራ ህዝብ የተደገሰለት ድግስ አደገኛ መሆኑን ስለተረዱ ብቻ የኢትዮጵያን ህዝብ ያካተተ የአማራ ድርጅት (ተገደው በግድ በዘር መደራጀት ስለነበረባቸው ያለበለዚያ ግን እውቅና በወያኔ ስለተነፈጉ) ሲመሰርቱ አሁንም ፕሮፌሰር መስፍን በአማራ ላይ የሚፈፀመውን በደል ጆሮ ዳባ ልበስ ብለው አማራ የሚባል ነገድ የለም በሚል ጎዳና ስለተሰለፉ ህዝቡ በተለይም አማራው በአንድ ልብ እንዳይቆም በደካማ ጎኑ ስለመጡበት ኢትዮጵያን እያለ ከተገንጣይና ካስገንጣይ ጉያ እንዳይወጣና ጠንክሮ እንዳይታገል እውቅናቸውን ተጠቅመው በሚያንፀባርቁት የተዛባ አስተሳሰብ ህዝብም አገራችንም ተጎድተዋል ።
የቅንጅት መሪዎች በፈጠሩት አለመግባባት የኢትዮጵያ ህዝብ ፕሮፌሰር መስፍን አስታራቂ ሀሳብ አምጠተው ቅራኔውን ይፈቱታል ተብለው ሲጠበቁ እሳቸው ለማንም የማይበጅ ምክር በመምከራቸው ህዝብ የሳቸውን ቃል ተከትሎ ቅንጅትን እንዳያንሰራራ አድርጎ አፈረሰ።
«አማራ የለም» ከማለት አልፈው «በአርባ ጉጉ የሞተው ኦሮሞ ነው» ማለታቸው ሟች በሌለበት ገዳይ አይኖርምና የአማራን ደም ደመከልብ እንዲሆን ትብብር አድርገዋል።
ለመሆኑ እኔ እንዲህ ብዬ እንደማስብና የዚህ አይነት ሀሳብ ያለን በሚሊዮን የምንቆጠር አማሮች መሆናችንን ቢረዱ ምን ይላሉ?
አቶ አንተነህ እርሰዎ እንዳሉት ፕሮፌሰር መስፍን «ትልቅ ሰው፣ አዋቂ፣ የተከበሩና የእድሜ ባለፀጋ» በሚለው ቃል እስማማለሁ። ነገር ግን «ደምመላሽ» የሚለው ቃል ሲወጣ አባባሉ ከቅንነት ይሆናል የሚል ግምት ቢኖረኝም የተጠና አልመሰለኝም። «ደምመላሽ» መሆኑ ቀርቶ የአማራ ህዝብ ተቆርቋሪ አለመሆናቸውን ደሙ ደመ ከልብ ሁኖ አንዲቀር የተወሰነበት «የለህምና አልሞትክም» የሚሉት አማራ ይመሰክራል።
አቶ አንተነህ ስለ አቶ ተክሌና ስለእርስዎ ግንኙነት ሲፅፉ ” ….ብዙ ህዝብ በሚርመሰመስበት የደመቀ በአል መሃል የሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት መሪ የሆኑትን አቶ ተክሌ የሻውን አገኘኋቸው። ደስ ብሎኝ ራሴን ካስተዋወቅሁ በኋላ በወጋችን መሃል በቅርቡ ከወጣው መግለጫቸው አምስት ገጽ እውነት ውስጥ ጨዋነት የጎደለው ስድብ ተገቢ እንዳልነበር ነገርኳቸው። የሰማሁት መልስና ለፕሮፌሰሩ ያላቸው ጥላቻ አስደነገጠኝ። ለአማራው ህዝብ መብት ቆሜያለሁ ብለው አደባባይ የወጡ እኒህ ሰው አንዱን ታላቅ ወገናቸውን በሰብዕናቸው ገብተው ሲዘልፉ መመልከት ዓላማቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ሆኖ አገኘሁት። ስልሳዎቹ ውስጥ የሚሆኑ እኒህ አዛውንት ሌላው በእድሜ፣ በእውቀትና በተመክሮ ለሚበልጧቸው ክቡር ሰው የሚሰጠውን የጨዋ አማራ ባህል ከውስጣቸው አላየሁም። ስለሆነም ውይይቴን ብቀጥል የበለጠ ህሊና የሚያቆስል ነገር እንደምሰማ በመገመት ተሰናበትኋቸው። ” ሲሉ አስነብበውናል።
አቶ ተክሌን ሲያገኙ ደስ መሰኘዎትን በዚህ አንቀፅ ቢገልፁም ከላይ በአንቀፅ 4 ላይ ደግሞ ”…የብዙዎችን ላቆየውና በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ካንድ ወገን የሚሰነዘረው ከባህላችን ውጭ የሆነ ዓላማው ግልጽ ያልሆነ ስድ በሚያሰኝ የመንገድ አዳሪ ቋንቋ የስድብ ውርጅብኝ በኒህ አዛውንት አባት ላይ ሲወርድባቸው ዝም ብሎ መመልከቱ ለህሊና ይከብዳል…” ሲሉ ቁጭትዎንና ቁጣዎትን ገልፀው ስለነበር አቶ ተክሌን ሲያገኙ የተደሰቱት ለምን እንደሆነ ለመረዳት አዋቂ መጠየቅ አያስፈልግም።
እንደርስዎ አገላለፅ አቶ ተክሌ በጥላቻ የተሞሉና ስነምግባር የጎደላቸው እንደሆኑ ተርከዋል። ለነገሩ አቶ ተክሌ ራሳቸውን መከላከል ስለሚችሉ አስፈላጊ ሆኖ ከታያቸው መልስ የሚሰጡበት ጉዳይ ይሆናል። ነገር ግን እኔን ያልገባኝ ነገር አቶ ተክሌ ጋር ስትነጋገሩ የተናገሩት ቃል አፀያፊ ከሆነ ቃላቶቹን በፅሁፍዎ ላይ በማስፈር መግለጫውን በተቹበት መልክ ቢያካትቱት የአንባቢውን የግንዛቤ አድማስ ስለሚያሰፉት አንባቢው በራሱ ሚዛን መዝኖ ለፍርድ በበቃ ነበር።
በተረፈ« በጥላቻ የተሞሉና ስነምግባር የጎደላቸው ስለሆኑ ለአማራው ህዝብ መቆማቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ሆኖ አገኘሁት» የሚለው ”ሾላ በደፈና” አባባልዎ፥ «ሞረሽ ወገኔ አላስፈላጊ ድርጅት ነው። አማራ መደራጀት የለበትም» ከማለት ተለይቶ አይታይም። ስድብ ነውር ከሆነ ነውር መሆን ያለበት ከተሳዳቢው አንደበት ሲወጣ እንጅ ተቀባዩ ላይ የሚያደርሰው ጫና ወይም የተሰዳቢው ማንነት ሚዛን ውስጥ እየተቀመጠ አለመሆኑን መዘንጋትዎ አስገርሞኛል። እንዲህ ለማለት ያበቃኝ ደግሞ እርስዎ ”ክደትና መሳት” የሚለውን ቃል በማስረጃነት በማቅረብ ያስነበበውን የሞረሽን መግለጫ ስድብ ካሉ በኋላ በአቶ ተክሌና በሞረሽ ላይ ”ስድ በሚያሰኝ” ”የመንደር አዳሪ ቋንቋ” በማለት አቶ ተክሌን «ስድ» ከማለት አልፎ የሞረሽ ወገኔን አባላትና ደጋፊ ሁሉ «የስድ ስብስብ» እንደማለት የስድብ ውርጅብኝ ሲያዘንቡ ውነቱን ተናገርኩ እንጅ አልተሳደብኩም ሊሉ ይሆን?
ለነገሩ «የወደቀ ግንድ ምሳር ይበዛበታል» ነውና የሚሞተው የሚሳደደው የሚፈናቀለው አማራ እንደ ህዝብ ከ34 ሚሊዮን በላይ ሲሆን፣ ያ ህዝብ ለሚደርስበት በደል ተጠያቂ እንኳዋን እንዳይኖር «የለህም» እያሉ አደባባይ ወጥተው የሚሞግቱት ፕሮፌሰር መስፍን ሳይወቀሱ፣ «የለም ማለት ስህተት ነው በደል የሚደርስበት ወገን ከተካደ በደል ፈፃሚ ነፃ ይሆናል» ያለውን ወገን ለማዳከም ብዕር ማንሳት የሚያሳዝን ክስተት ነው። ለነገሩ እርሰዎ የኢትዮጵያ ጀግኖች ብለው በፅሁፍዎ የደረደሩዋቸው ሁሉም ለኢትዮጵያ አንድነት የተሰለፉ ጀግኖች ናቸው ብየ ስለማላስብ የእርስዎም ሰልፍ ከወዴት እንደሆነ አልገባኝምና ልተወው።
ለማንኛውም እርስዎ ከፐሮፌሰር መስፍን በተለየ «አማራ» የሚባል ነገድ እንዳለና ያም ወገን የተለየ ግፍ እየተፈፀመበት እንደሆነ ውነቱን በመመስከርዎ አድናቆቴን ልቸርዎት እወዳለሁ። ምክንያቱም እርስዎ በፕሮፌሰር መስፍን ማንነትና ፍቅር ስለተሸነፉ፣ የሞረሽ ወገኔን መግለጫ በማጣጣልና «ፕሮፌሰርን በካሀዲነት ወነጀሉ» ብሎ የፕሮፌሰርን ስህተት ማደባበስ ብሎም ያላግባብ ደሙ የሚፈስ ወገን እንዳለ ማመን የተሳነውን ሰው «ደምመላሽ» በማለት ማሞካሸትዎ እንዳለ ሁኖ፣ «በፕሮፌሰር ተፃራሪ አማራ አለ፣ በደልም እየተፈፀመበት ነው፤» ብለው ሲቆሙ ሳይ ታዲያ ምነው የሚያከብሩዋቸውና የሚያደንቋቸው ፕሮፌሰር ሲሳሳቱ በክብር እንዲያስተካክሉ አልጠየቋቸውም ያሰኛል።
እንደእኔ ግንዛቤ ፕሮፌሰር መስፍን በየጊዜው ብዙ ጠቃሚም ጎጅም ፅሁፍ ለንባብ አብቅተዋል። ለዚህም የኢትዮጵያን ህዝብ «ሆዳም» ብለው መዝለፋቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው። ለአማራውም «አለሁ» ሲል «የለህም»፣ «እየተገደልኩ ነው» ሲል «የት አለህና?» በማለት 23 አመት ሞግተውታልና ለመግለጫው መልስ የሚያስፈልግ ቢሆን እርስዎም እንደገለፁት እራሳቸው ፕሮፌሰር መልስ መስጠት ስለሚችሉ የእርስዎ ጥብቅና ” የምጣዱ እያለ የንቅቡ ተንጣጣ” እንድል ዳርጎኛል። ፕሮፌሰር መስፍን ነገዱን ሁሉ እየጠሩ እውቅና ሲሰጡ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ «አማራ የሚባል ነገድ የለም» ማለታቸው ግን እንቆቅልሽ ነው በማለት ሀሳቤን እቋጫለሁ።
ፀሀፊዋን agereamanu@yahoo.com ማግኘት ይቻላል።

No comments:

Post a Comment