Tuesday, November 11, 2014

ዝምታው ለምን ነው? (አንተነህ መርዕድ)

ዝምታው ለምን ነው?
ኢትዮጵያ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለችው።
  • መንግስት እንደድሮው መግዛት ተስኖታል
  • ህዝቡም እንደድሮው መገዛት ታክቶታል
  • የተቃዋሚው ቋንቋም እንደባቢሎኖች የተከፋፈለበት ወቅት ላይ ነን
  • ከዚያም ብሶ ሚድያው ታፍኗል።
ትግሉን በተደራጀ መልክ ዳር የሚያደርስ ጠርቶ ባልወጣበት ሁኔታ ህዝባዊ ዓመጽ ሊፈነዳ ጫፍ ላይ መድረሱን ለማወቅ ሊቅነት የሚጠይቅ አልሆነም። በዚህ ሁኔታ ዐመጽ ከተነሳም የሚከተለው ትርምስና እልቂት ቀላል ስላይደለ ንፁህ ህሊና ያለው ሁሉ በግልፅ ታይቶት መፍራት አለበት። ይህ ፍርሃት በጎ ፍርሃት ሊሆን የሚችለው ወደ መፍትሄው መሄድ ካስቻለን ነው።
በእንደዚህ ዓይነት ፈታኝ ወቅት ነፃ ሚድያ ግዙፍ ሚና አለው።
  • ህዝብ ተገቢ መረጃ እንዲኖረውና እርምጃው በእውቀት ላይ የተመሰረተ እንዲሆን በማድረግ
  • በእንደዚህ ዓይነት ቀውጢ ወቅት ብቅ የሚሉ የበግ ለምድ የለበሱ ተኩላዎች ህዝባዊ ትግሉን ወደ ተለየ አቅጣጫ እንዳይመሩትና ለሌላ ተስፋ አስቆራጭ ክስተት እንዳይዳርጉት በማጋለጥ (ይህ ለታሪካችን አዲስ አይደለም)
  • የህዝቡን የጋራ ብሶትና የጋራ ተስፋውን አጉልቶ በማውጣት ወደ ብሄራዊ መግባባት ለመድረስ መገናኛ ብዙሃን ከባድ ሃላፊነት አለባቸው።
ስለሆነም አምባገነን ስርዓቱ ሚድያውን ለማዳከም ያሰደደንና በሁሉም የዓለም ክፍል ተበትነንና ተደላድለን የምንኖር ሆንነ አሁንም በወከባው ውስጥ ያለነው ተረጋግተን የምንነጋገርበት ወቅት አሁን ነው። የሃሳብ ልዩነቶች ሊኖሩን ይችላሉ። እንዲያውም “የሃሳብ ልዩነቶች ለዘለዓለም ይኑሩ”የሚለውን መፈክር ልናነግበው የሚገባ ነው። ነገር ግን የሃሳብ ልዩነት መኖሩ የሃሳብ ግብይትን ያቆመው እለት የሃገር ውድቀት እሙን ነው። የሃሳብ ልዩነት የሃሳብን ግብይትና መቀራረብን ሊያቆመው አይገባም። (ኮሙኒኬት የማያደርጉ ኮሙኒኬተርስ) ከመሆን እንውጣ።
ሀገርን የማዳን ቃል ኪዳን በሁላችንም ዘንድ እንዳለ ይታወቃል። ችግሩ ማን ይጀምረውና እንዴት ይጀመር የሚለው ነው።
  • የታሰሩ ወንድሞቻችን የሚከፍሉትን መስዋዕትነት በፀጋ ቢቀበሉትም የቤተሰቦቻቸውን ጫና የማቃለል የሞራል ሃላፊነት አለብን።
  • በጎረቤት አገሮች በስደት የሚሰቃዩ የሙያ ባልደረቦቻችን ያሉበትን ሁኔታ ያለፍንበት ሁሉ እናውቀዋለን። በችግሮቻቸው መድረስ ይኖርብናል።
  • ከሁሉም በላይ ግን ማንም ሳያስገድደን ለራሳችን ቃልኪዳን የገባነው ህዝብን ተመጣጣኝ መረጃ የመስጠት ሥራ እዚህ ደርሶ አላበቃም። እንዲያውም ተፈላጊነቱ እየጎላ ነው።
“ተባበሩ ወይም ተሰባበሩ” የሚለው የህዝብ መፈክር ለተቃዋሚዎች ብቻ ሳይሆን ለጋዜጠኞችም ጭምር ነው። በነጠላ እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴ የማይናቅ ቢሆንም በጋራና በተቀናጀ እንደሚደረገው ፈጣንና አመርቂ ውጤት አያመጣም። አገሪቱ ያለችበት ፈታኝ ሁኔታ ፋታ የሚሰጥ ባለመሆኑ በተገኘው መንገድ ሁሉ ግንኙነቱ ይቀጥልና በህብረት ወደ አንድ አቅጣጫ እንንቀሳቀስ። ስለዚህም መነጋገር እንጀምር። “ባለቤት ካልጮኸ ጎረቤት አይደርስም” ነው ተረቱ። ህዝቡን እንዲረዳን የምንጠራው መጀመርያ ራሳችን ችግሩን አውቀን ስንንቀሳቀስ ነው። ለችግራችን እኛው መፍትሄ እንፈልግለትና በአገር ጉዳይም የማንናቅ የመፍትሄ አካል እንሁን። ዝምታው ለምን ነው?

No comments:

Post a Comment