Tuesday, August 11, 2015

አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ በእኔ ዕይታ

በአብርሃም በዕውቀት እርግጥ ነው ፕሮፌሰርን ለመተቼት የሚመጥን ቀርቶ ሊመጥን የሚጠጋ የዕውቀት ልክ ላይኖረኝ ይችላል፡፡ ለዚያውም ከፕሮፌሰርነታቸውም በላይ ሕይወት ያስተማራቸውንና በተቃውሞ ፖለቲካው ጫፍ የወጣ ዕውቅና ያላቸውን ፕሮፌሰር ጽሑፍ መንቀፍ በፌስቡክ ዳኞች በስቅላት ሁሉ ሊያስቀጣ ይችላል፡፡ ኧረ ራሳቸውም ሊሰቅሉኝ ባይችሉም ሊያሳቅሉኝ ይችላሉ፡፡ በእርግጠኝነት ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያምን ለመተቼት መሞከር የሚያስከትለውን ዘለፋና ነቀፌታ በሚገባ አውቀዋለሁ፡፡ ምክንያቱም እርሳቸው ከአገራችን ፊደላውያን መካከል ቁንጮ ናቸውና፡፡ ነገር ግን ፈርቶ ከመሞት ተናግሮ መሞት ይሻላል ብዬ ትችቴን ልቀጥል መሰለኝ? በቃ እንዲያውም ቀጠልኩ፡፡
ፕሮፌሰሩ ባለፈው ግንቦት ወር አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ የሚል መጽሐፍ ለገበያ አብቅተዋል፡፡ በነገራችን ላይ ፕሮፌሰር መስፍን በፈረንጅ ቋንቋ ሶስት አራት ‹‹ጆርናል›› ጽፈው የሚኮፈሱ ምሁራንን የሚያስከነዱ ቁጥራቸው በርከት ያሉ መጻሕፍትን ለኢትዮጵያውያን በራሳቸው ቋንቋ የሚጽፉ ሰው ናቸው፡፡ በዚህ ሥራቸው በእጅጉ አመሰግናቸዋለሁ፤ አደንቃቸዋለሁ፡፡ ሌሎቹ የአገራችን ፊደላውያን ቀደም ሲል እንደገለፅኩት ጥቂት ‹‹ጆርናሎችን›› በተለያዩ ርዕሶች ላይ ከመጻፋቸው ውጭ ለዚያውም ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውጭ አንባቢም ተጠቃሚም በሌላቸው ጭብጦች ላይ በአማርኛ ቋንቋ አንዳች ነገር ሲፅፉ አይታዩም፡፡ ለዚህም ነው ምሁራን ከማለት ተቆጥቤ ፊደላውያን የምላቸው፡፡ የፊደል እንጅ የተግባር ዕውቀት ስለሌላቸው፡፡ ወደ ተነሳሁበት የፕሮፌሰር መስፍን መጽሐፍ አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ ልመለስ፡፡ መጽሐፉ ዋነኛ ትኩረቱ ከዚህ በፊት ‹‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ›› በሚል ያሳተሙትንና በብዙዎቹ ዘንድ የተቃውሞ አቧራ ያስነሳውን መጽሐፍ ነቀፌታዎች ለማብራራትና አንዳንድ ተችዎችንም ልክ ለማስገባት የተፃፈ ይመስላል፡፡ በመጽሐፉ ገፅ 27 ሁለተኛው አንቀፅ ላይ ‹‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክን ስፅፍ በኢትዮጵያዊነቴ መንፈስ ተይዤ ነው፤ ይህንን መካድ አልችልም፤ ከሰማይ እንደወረደ ሰው ሆኜ ስለኢትዮጵያ ታሪክ መጻፍ እችላለሁ የሚል ኢትዮጵያዊ ታሪክ ጸሐፊ (ወይም የታሪክ ተመራማሪ) ካለ የሚናገረውን የሚያውቅ አይመስለኝም፤ ከኢትዮጵያዊ ትውልዴ፣ ከኢትዮጵያዊ አስተዳደጌና ስሜቴ፣ ከበርበሬው መፋጄትና ከቡናው ትኩስነት ራሴን ሙሉ በሙሉ አግልዬ ስለኢትዮጵያ መናገር እችላለሁ ብዬ አልዋሽም›› የሚሉት ፕሮፌሰሩ በእኔ ዕይታ የዚህ ዘመን ታሪክ ፅሐፊዎችም እንደ ድሮ ግለ-ታሪክ ፀሐፊዎች (chroniclers) ሁሉ ገለልተኞች (objective) አይደሉም እያሉ ነው የሚል ድምዳሜ ደርሻለሁ፡፡ ስለዚህ መጽሐፉ ከስሜታዊነት አልፀዳም፤ ታሪክ አይደለም፤ ከሽፏል፡፡ በእርግጥ መጽሐፉ እርሳቸው ስለመክሸፍ የሰጡትን ትርጓሜና የክሽፈታችን ማስረጃዎች ናቸው ያሏቸውን ሀሳቦች በጥልቀት ለማብራራት ይሞክራል፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን እንደሚሉት በተለይ ዓድዋ ላይ በዓፄ ምኒልክ ዘመን ድል ያደረግነውና ዓለምን ያስደመምንበት ጣሊያን ከአርባ ዓመታት ዝግጅት በኋላ በዓፄ ኃይለስላሴ ዘመን ከ1928 ዓ.ም እስከ 1933ዓ.ም ድረስ ድል አድርጎናል፤ እኛ ግን በአርባ ዓመታት ውስጥ ከመሻሻል ይልቅ ስንበሰብስ ቆይተናል ይላሉ፡፡ እዚህ ላይ ለፕሮፌሰር ጥያቄ ላንሳ፤ ‹‹ዓድዋ ላይ ጣሊያንን ያሸነፍነው በስልጣኔና በጦር መሳሪያ በልጠነው ስለነበር ነው?›› እንደኔ አይደለም፡፡ ይህ ለፕሮፌሰር ይጠፋቸዋል ብዬ ባልጠብቅም ጳውሎስ ኞኞ ‹‹አጤ ምኒልክ›› በሚል ባሳተመው መጽሐፍ ገፅ 159 ጀምሮ እንዳስቀመጠው ኢትዮጵያውያን ወደ ዓድዋ ዘመቻ ሲሄዱ 42 መድፎች ብቻ ነበሯቸው፡፡ ይህ ቁጥር ከኢጣሊያ ዘመናዊ የተራራ መድፍ ጋር አይወዳደርም ሲልም ይገልፃል፡፡ በሰራዊት ቁጥር ደረጃ በአንፃሩ ኢትዮጵያውያን እጅግ ብዙ ነበሩ፡ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/45770#sthash.MXsHvl9E.dpuf


adafne

No comments:

Post a Comment