Thursday, December 4, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ – (ከደብረጊዮርጊስ)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን! ማኅበረ ቅዱሳን Nov. 23 2014 E.C ላውጣፍ ጽሑፍ መልስ።
ሁሌ እራስን ከፍ ከፍ ማድረግ ብቻ! እንዴት ነው ነገሩ? ቀኝህ የምትሰራውን ግራህ አትይ፣ በስውር ለሰራኽው በግልጽ ጌታ ይከፍለሃል፣ ራሱን ከፍ ከፍ ያሚያደርግ ዝቅ ዝቅ ይላል እየተበለ ሲነገርና ትምኅርት ሲሰጥ ሰምተናል። ይህ ለማኅበረ ቅዱሳን አይሰራም እንዴ ??? ሁል ጊዜ እኔ የምሰራው የጽድቅ ሥራ ነው፣ እኛ ተሳስተን አናውቅም፣ እኛ ከሌለን ቤተክርስቲያን አትኖርም ወዘተ። በተቃራኒው እኛንየተቸ መናፍቅ ነው፣ መናፍቅ ካልሆነ “ተሃድሶ” ፕሮቴስታንት ነው፣ ለጥቅም የቆመ አማሳኝ ነው ወዘተ።
mahibere-kidusan-logo
ግርም ይላል!!! እውነቱን ስንነጋገር ማኅበረ ቅዱሳን የሰራቸው ብዙ ጥሩ ነገሮች አሉ። ግን እነኝህን በጎ ሥራዎች ሊመሰክርለት የሚገባው ራሱ አይደለም። እንዴት ራሱ ሰርቶ ለራሱ ምስክርነት ይሰጣል??? ጥሩ ስለመሥራቱ ሊመሰክሩ የሚገባቸው ሌሎች ናቸው። ደግሞም ጥሩ የሚመሰክሩ እንዳሉም ስህተቱንና
ሊታረም የሚገባውን የሚተቹም እንዳሉና እንደሚኖሩ ማወቅ ያሻል። ነገር ግን እነኝህ ተቺዎች በሙሉ መናፍቃን “ተሐድሶ” ፕሮቴስታንት ወዘተ አይደሉም። ከማኅበሩ ባላነሰ መናፍቃንን ከሚተቹና ጸረ መናፍቅ ነኝም ብዬ አስባለሁ ስው የሚለኝን ባላውቅም። እናም የዚህ ጽሑፍ/ትችት አቅራቢ ጸረ መናፍቅ
ነው።
እንደ እኔ እይታ ምንም እንኳን ማኅበረ ቅዱሳን የሰራቸው በጎ ነገሮች ቢኖሩም ብዙ ሊታረሙና ሊሻሻሉ የሚገባቸው መሠረታዊ ለውጥ ጭምር ሳይቀር ሊያደርግባቸው የሚገቡ ጉልህ ጉድለቶች አሉበት። ለምሳሌ አደረጃጀቱን በተመለከተ የቤተክርስቲያንን ማዕከላዊነት የሚፃረር ነው። ባለፈው በቤተ ክህነቱ
ስብሰባ እንደተገለጸው ሁለት ቤተክርስቲያን ያለ ያህል ቤተክህነትን አክሎ በራሱ መዋቅር ዘርግቶ የሚያደርገው እንቅስቃሴ በርግጥም ከጥቅሙ ጉዳቱ ማመዘን ብቻ ሳይሆን የተሳሳተም ነው። ሊሆን የሚገባው በየከፍተኛ የትምኅርት ተቋማት ተማሪዎች እንደልባቸው ቤተክርስቲያን እና የቤተክርስቲያን
ትምህርት ስለማያገኙ በዛ ዙሪያ የቤተክርስቲያን ትምህርት ሊያገኙ የሚችሉበትን ሁኔታ ላይ ብቻ መወሰን ይገባዋል ባይ ነኝ። ከከፍተኛ ተቋማት የትምህርት ጊዜ በኋላ ተማሪዎቹ/ተመራቂዎቹ ወደ ሕብረተሰቡ ሲቀላቀሉ እንደማንኛውም የቤተክርስቲያኗ አባል በሰበካ ጉባኤ እና በሰንበት ትምህርት ቤት እየታቀፉ
በሚችሉት ሁሉ ቤተክርስቲያንን ማገልገል ቢችሉ ጥሩ ነው። ከከፍተኛ ትምህርት በኋላ ልክ እንደቤተክህነት ተደራጅቶ የራስ ማኅበርን ስለማጠናከርና የራስን ጉባዔያት ማካሔድ ለዘለቂታው ቤተክርስቲያን የራሷ የሆነውን ማዕከላዊ አመራር እንዳይጠናከር ማድረግ ነው። በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በእውቀትና በሚችሉት ሁሉ ሰበካ ጉባዔያትን፣ ሰንበት ትምኅረት ቤቶችን፣ ወረዳ ቤተክህነትን፣ ሃገረ ሥብከትን ብሎም ዋናውን ጠቅላይ ቤተክህነትን እና መምሪያዎችን ማጠናከር እንጂ ለራስ ሌላ ቤተክህነት ሆኖ መንቀሳቀስ ቤተክርስቲያንን ያዳክማል እንጂ አያሳድግም። ሌሎችንም ውሻ በቀደደው… እንዲሉ ተመሳሳይ ማኅበራት እየተፈጠሩ እንዲሄዱና ሁሉም የራሱን ጥቅምና አላማ ላይ እንደልቡ እንዲያተኩር ያደርገዋል። አንድ ብቻ ሳይሆን አስራ አንድ ከዛም በላይ ማኅበራት በዚህ መልክ የመደራጅት መብት አላቸውና። ስለሆነም ማኅበረ ቅዱሳን በእውነት ለቤተክርስቲያን መጠናከር እና እድገት ካሰበ ራሱን ማስተካከል አለበት።

ሌላው የማኅበሩ ስህተት ብዙ ጊዜ አህያውን ፈርቶ ዳውላን የሚሉት አይነት ነው። በቅዱሳን ሥም ተሰባስቦ ስለቤተክርስቲያን ይገደናል ካሉ ግለሰብም ይሁን ድርጅት ወይንም መንግስት በቤተክርስቲያን ይዞታ፣ መብትና ክብር ላይ ጉዳት ሲያደርስ በእኩል ጥብቅናን ለቤተክርስቲያን ማሳየት ይገባል። በዚህ ዙሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ከአሥር ለሚታረም ጥያቄ ሁለት ከአሥር ብቻ ያገኝ ይሆናል። ቅዱሳን እስከ ሞት ድረስ አላውያንን ገሥጸው ለእምነታቸው ምስክር ሆነዋል እንጂ አድርባይና ፈሪ ሆነው ከእምነታቸውና ከኃይማኖታቸው ክብር አጉዳፊዎች ጋር አላበሩም። የቤተክርስቲያኗ ታላቅ ገዳም ሲደፈር ገዳማዊያኑ የድረሱልን ጥሪ ሲያሰሙ፣ አላውያን መሪዎች ቤተክርስቲያንን ሲያንንቋሽሹ እና አከርካሪውን ሰብረነዋል በማለት ሲያላግጡ እንደ አንድ ትልቅ የቤተክርስቲያን ማኅበር እንዴት ዝም ይባላል? ይህም ወይ እንደ እስክንድር ተዋጋ ወይ የእስክንድርን ስም መልስ የሚለውን አባባል ያስታውሳል።
ሦስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ስህተት ከላይ የተጠቅስው የአደረጃጀት ውጤት ያስከተለው ነው። ይህም ለቤተክርስቲያን ዘላቂና መሠረታዊ የሆኑ ተቋማትን በጥራት ከመስራትና ለቤተክርስቲያኗ እድገት አስተዋስዖ የሚያደርጉ ሥራዎች ላይ ከማተኮር ይልቅ ለራስ/ለስጋ የሚመቹ የጽ/ቤት ግንባታዎች እና የንግድ ሥራዎች ላይ ማተኮሩ ቆሜለታለሁ ከሚለው መንፈሳዊ አገልግሎት በተለይም ጠበቅ ያለ የክርስትና ሕይወት ነው የምንመራው እንዲሉ ከሆኑት አባላቱ ሁኔታ ጋር ፈጽሞ የተለያየ ነው። ጽድቅ ከራስ ቆርሶና ራስን ጎድቶ ለሌላው እንደራስ አስቦ የራስን እንኳን አካፍሎ የሚገኝ ወይንም የሚኖር ሆኖ ሳለ የግሉ ቀርቶ በጋራ እንኳን ለሚደረገው ነገር ቅድሚያ ለእኛ በሚል አካሔድ የትም ወድቀው ለሚታዩት ወገኖች የሚረዳ ጓለማውታ፣ የአረጋውያን መጦሪያ፣ የእኔ ብጤ ልጆች ማስተማሪያና ማሳደጊያ ከመሥራት ይልቅ ለራስ የሚመቹ ነገሮችን ማስቀደሙ ማኅበሩን የሚያስተቸው ነው። ከዚህም ሌላ ቤተክህነቱ ሊሰራው የሚገባውን ሥራ እንዳይሰራና ፍፋላፊነቱን እንዳይወጣ መሻሻል እንዳያሳይ ተጽ እኖ ያደርጋል።
እንደቤተክህነት ደመወዝ ከፋይ መሆን ያውም ያለ ቤተክርስቲያኗ ገቢና ወጪ ካርኒ ወጪ ለራስ ደጋፊዎችን ለማከማቸት ካልሆን በስተቀር ለቤተክርስቲአን እድገትና ለውጥ አያመጣም። እድገት የሚያመጣው የቤተክህነቱን አድባራትና ገዳማት መምሪያ ማጠናከ ነውና። አራተኛው ስህተት ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ይመለከታል ። መቼም አሁን ይህ የቤተክርስቲያን ሥርዓት እንዲህ ሆኖ ቢሻሻል ይሻላል ቢባል ይኼማ መናፍቅ ነው ተሃድሶ ምናም ነው እንደሚባል አልጠራጠርም።
እውነታው ግን አንዳንድ የማኅበሩ አባላት የሆኑ ሰዎች ከተለምዶው/ ከቀኖና ቤተክርስቲያን ውጪ ዲያቆናት፣ ቀሳውስት ሲሆኑ እናያለን እንሰማለን። መሆናቸው ብቻ ሳይሆን የሚገርመው የሆኑትን ሆነው ለመገኘት ብዙም ጥረት ሲያደርጉ አለመታየታቸው ነው። አንዳንዴም በድፍረት ያልተማሩትን እና
የማያውቁትን ሙያ በሚያሳፍር መልኩ በአደባባይ ሲያበላሹ ይስተዋላሉ። ይህም ሊታረም የሚገባው ነው።
ሌላውና ትልቁ የማኅበሩ ድክመት ደግሞ በቤተክርስቲያን ጉዞ ውስጥ በየዘመኑ የሚፈጠሩ ፈተኛዎች እና ውጣ ውረዶች መኖራቸው እየታወቀ ልክ ዛሬ የመጡና የተፈጠሩ ይመስል ትናንሽ ነገሮችን ከሚገባው በላይ በማጋነን፣ ባለማወቅና በተለያዩ ምክንያቶች የንጽህት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን አስተምህሮ
ባለመረዳት ከቤተክርስቲያኗ አስተምህሮና ይትባሃል የሚወጡትን በፍቅርና በጥበብ ወደ ቤተክርስቲያኗ ከመመለስ ይልቅ አጋኖ አጋኖ እንዳልነበሩ ማድረጉ ነው። ይህም አንቺ ማነሽና ማንን ታሚያለሽ ያሰኘዋል።
ለምሳሌ ኦርቶዶክሳዊ መዝሙራትን በተመለከተ ያለውን ክፍተት በመሙላት ለምእመናኑ አማራጭ ከማቅርብ ይልቅ ያለውን ክፍተት የተገነዘቡ በክፍተቱ ለመጠቀም እና ያለባቸውን ሥጋዊ/ የኑሮ ችግር ለማቃለል የሚያደርጉትን ሩጫ መቃወም ብቻ ፋይዳ የሌለው መሆኑንን በተግባር እያየነው ነው። በጣም
ብዙ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ሆነው ጥሩ ያሬዳዊ መዝሙራትን መዘመር የሚችሉና ክፍተቱን መሙላት የሚችሉ ወጣቶችን በማኅበሩ መመሪያ መሠረት በግል መዝሙር ማሳተም አይፈቀድም በሚል አንድ ሞኝ ያሰረውን እንደተረቱ ሺዎች ሊፈቱት ባለመቻላቸው ይኽው ብዙ ከአለማዊ ዘፈን የተወሰዱ ዜማዎችና ሥጋዊ ነገር ላይ ብቻ ያተኮሩ መዝሙራዊ ዘፈኖች እስከ ቤተመቅደስ ድረስ ደርሰው ማንም ሊቆጣጠረው ከሚችለው በላይ ሆነዋል። በተቀደሰው ሥፍራ የረከሰው ነገር ቆሞ ሲያይ አንባቢው ያስተውል የሚለውም ትንቢት የተፈጸመ ይመስላል።
ከዘረዘርኩት የሚበልጡትን ትቼ ይህን የመጨረሻ እና በእኛ ትውልድ ስለተከሰተው ታላቅ የቤተክርስቲያን ፈተና ማኅበረ ቅዱሳን የያዘውን ፈጽሞ የተሳሳተ እና ከኃይማኖት፣ ከታሪክ እና ከእውነት ጋር የተቃረነ አቋም ባጭሩ ላንሳ።
አሁን ሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ስልጣን በያዘ ጊዜ ቀድሞ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤና በአብላጫ ድምጽ ለፕትርክና የተመረጡት 4ኛው ፓትርያርክ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ከስልጣናቸው ሲባረሩ የተፈጸመውን ነገር እውነቱን እና አሉባልታውን መርምሮና አውቆ የጠራ አቋም መያዝ ሲገባ ለእኛ ከተመቸን ስለሥርዓተ ቤተክርስቲያን የራሱ ጉዳይ በሚል የተፈጠረው ችግር እንዲባባስ የማኅበሩ ጭፍን አቋም ቤተክርስቲያንን ጎድቷል።
በጊዜው አሞኛል ብለው ለቀዋል የሚል ዜና በጋዜጣ ከመውጣቱ በስተቀር አሞኛል ሲሉ የተናገሩት ድምጽም ሆነ የጻፉት ደብዳቤ አልተሰማም አልታየም። ይህንንም ካሉ ወይንም ከፃፉ በኋላ እንደገና ልመለስ ሲሉ አንዴ ከለቀቁ አይቻልም ተብሎ ሌላ ተሾመበት የሚል ወሬ 23 አመት ይወራል። ከሁሉ የሚገርመው በቤተክርስቲያኗ ሕግ መንፈሳዊ ላይ አንድ ፓትርያርክ ከስልጣኑ የሚተካው ሲሞት ወይንም ለሞት የሚያበቃው ህመም ሲያጋጥመው ነው ይላል። ለሞት የማያበቃው ህመም ቢያጋጥመው ግን ከህመሙ እስኪፈወስ በቦታው አቃቢ ተሾሙ ከሕመሙ ሲፈወስ ሊመለስ ይችላል ልድገመው ሊመለስ ይችላል ነው የሚለው ሕጉ። የሚድን በሽታ የያዘው ስልጣን ከመያዝ ሊከለክል አይገባም ይላል። እኝህ አባት አሞኛል ብለው ለቀቁ ደሞ ልመለስ አሉ የሚለው ክስ እውነት እንኳን ቢሆን ከቤተክርስቲያኗ ሕግ አንጻር እርሳቸው ያደረጉትን አንዳች ስህተት አያሳይም። ለቀውም ከሆነ እንኳን ሊመለሱ መብት አላቸውና!
እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ማኅበሩ በጭፍን ጠመንጃ ተገኑ ከሆነ ለጊዜው በሥጋ ሃይለኛ መስሎ ከታየው ጋር መቆሙና ቢያንስ የሆነው ሆኗል ከዚህ በኋል እንኳን እርቅና ሰላም ይውረድ አለማለቱ ነው። እንዲያውም በዚህ ዙሪያ በሚደረጉ የማጥላላትና በወደቀ ዛፍ ላይ ምሳር የማብዛት ድርጊት በቀጥታ ሲሳተፍ
በተደጋጋሚ ተስተውሏል። የመጀመሪያው ጥፋት ሳያንስም ለሁለኛ ጊዜ ይህ ጥፋት ሲደገም እርቅና ሰላም ይቅደም ከማለት ይልቅ ማኅበሩ አስመራጭ ኮሚቴ ውስጥ ገብቶ ተሳታፊ መሆኑ ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ የሚያሰኘው ነው። ስለቤተክርስቲያን አንድነት እድገትና ሰላም የሚገደው ማኅበር መጀመሪያ በጭፍን አይወግንም። ኋላም እርቅና ሰላም እንዲመጣ የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል እንጂ ያወጣው ያውጣው አይልም። ለጊዜው ጨረስኩ። እግዚአብሔር በሰጠን ጊዜ ካልተማርን እርሱ ራሱ በጊዜ ያስተምረናል።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

No comments:

Post a Comment